ኢዴፓ ግንቦት 30 ቀን 2001 ዓ.ም በደቡብ ክልል በሀዋሳ ከተማ ያካሄደው ሕዝባዊ ስብሰባ ውጤታማ ሆኖ መጠናቀቁን ከስፍራው የደረሰን ዜና አመለከተ። በሀዋሳ ከተማ አውቶቡስ ተራ አጠገብ በሚገኘው "ዳግም ጅምናዚየም" በተባለ አዳራሽ ከጥዋቱ 3፡00 ሰዓት እስከ ቀኑ 7፡30 ሰዓት ድረስ በተካሄደው ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ ቁጥሩ ከ1200 እስከ 1500 የሚሆን ሕዝብ በስብሰባው ላይ ተካፋይ መሆኑም ታውቋል።
የስብሰባው ተካፋዮች ከሀዋሳ ከተማ ብቻ ሳይሆን በከተማዋ ዙሪያ ከሚገኙ አነስተኛ የዞንና የወረዳ ከተሞች ማለትም፤ ከዲላ፣ ከአለታ ወንዶ፣ ከሻሸመኔ፣ ከይርጋ ዓለም፣ ከአላባና ከዝዋይ ከተሞች ጭምር እንደመጡ ታውቋል። የስብሰባው ተካፋዮች በኢዴፓ ላይ ያላቸውን ቅሬታ፣ ድጋፍና ተቃውሞ በነፃነት አቅርበው በፓርቲው ፕሬዚዳንት በአቶ ልደቱ አያሌውና በሌሎች ከፍተኛ አመራር አባላት ተገቢው ምላሽ ተሰጥቷል።












