መንግስት ለፖለቲካ ፓርቲዎች የሚሰጠው የፋይናንስ ድጋፍ የሚከፋፈልበት ረቂቅ ደንብ በኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ጽ/ቤት አማካይነት ተዘጋጅቶ ፓርቲዎች እንዲወያዩበት በቀረበው ጥሪ መሰረት ኢዴፓ የማሻሻያ ሃሳብ ማቅረቡን የፓርቲው ዋና ጸሐፊ አቶ ሙሼ ሰሙ ገለጹ።የኢዴፓ ተወካይ በውይይቱ ላይ ተገኝተው አስተያየትና ጥያቄ ያቀረቡ መሆናቸውንና፣ ተጨማሪ ማሻሻያዎች ካሉ በጽሑፍ እንዲቀርብ በተገለጸው መሰረት ፓርቲው ያዘጋጀው ማሻሻያ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ጽ/ቤት የተላከ መሆኑን አቶ ሙሼ አስረድተዋል።




የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ፕሬዚዳንት አቶ ልደቱ አያሌው በአዲስ አበባ ከሚገኙ የሁለት አገሮች አምባሳደሮች ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ከፓርቲው የውጭ ጉዳይ ዘርፍ ያገኘነው መረጃ አመለከተ። አቶ ልደቱ ውይይት ያደረጉት ከኖርዌይ አምባሳደር እና ከጀርመን አምባሳደርና የፖለቲካ ጉዳይ ኃላፊ ጋር መሆኑንም የዜና ምንጫችን ጨምሮ ገልጿል።










